Sunday, July 29, 2018

የፍቅር ጮራ

ባጨለሙት ሰማይ
በገዙት ምድር ላይ
የክፋት ዘር ዘርተው
አንዱን ሐረግ ባንዱ እየጠመዘዙ
                          ዘመናት ተጓዙ
የቀመሩት ቀመር
የሸረቡት ሴራ ድንግዝግዝ ፈጠረ
አንዱ ግንድ ከሌላው ፍትጊያ ጀመረ
ሐገር ጽልመት ዋጣት
ጨለማ ነገሰ
ሌባው ተመችቶት የልቡ ደረሰ

ጨለማ ነው ብሎ እንዳሻው ሲጋልብ
ያሻውን ሲያደርግ
አንዱ አንዱን እንዲጥል ሲያፋትግ ሲያፋትግ

ከፍትጊያው መሃል እሳት ብልጭ አለ
ብርሃን ፈነጠቀ
እውነተኛው ጠላት ተለየ ታወቀ
በደም መስተፋቅር ሐረግ ተዋደደ
አንድነት ነገሰ ሰላም ተወለደ
የነፃነት ፋና ጮራ ፈነጠቀ
ሰውነት ከበረ ሰውነት ደመቀ

No comments:

Post a Comment